ቻይና የንጹህ ኃይል ምንጭ የሆነውን የሃይድሮጂን ጣቢያ በመገንባት ከዓለም ቀዳሚ መሆኗ ተገለጸ።

ቻይና በዓለም ላይ ትልቁን የሃይድሮጂን ጋዝ ማደያ ጣቢያዎችን በመገንባት በዓለም አቀፍ የሃይድሮጂን ውድድር ግንባር ቀደም ሆናለች።

ሀገሪቱ ባላት ከፍተኛ ንፁህ ኃይልን ሥራ ላይ የማዋል ግብ እና በዘርፉም በጉልህ መዋዕለ ንዋይ በማፍሰስ የካርበን ዜሮ-ልቀትን ተግባራዊ ለማድረግ መንገድ እየጠረገች ነው ተብሏል።

የቻይና ታዳሽ ኃይል ማህበረሰብ ምክትል ፕሬዚዳንት ጂያንግ ሊጁን እንዳሉት፤ ቻይና ከ400 በላይ የሃይድሮጂን ጋዝ ማደያ ጣቢያዎችን ገንብታለች።

ይህም በዓለም በሃይድሮጂን ጋዝ ማደያዎች አንደኛ ደረጃ ላይ እንድትገኝ እንዳደረጋት በመግለፅ እስካሁንም 280ዎቹ ስራ መጀመራቸውን ተናግረዋል።

የቻይና ሃይድሮጅን አሊያንስ በ2025 የቻይና ሃይድሮጂን ኢነርጂ ኢንዱስትሪ ምርት ዋጋ አንድ ትሪሊየን ዩዋን ይደርሳል ብሏል።

የሃይድሮጂን ኢነርጂ ከቻይና የኃይል ስርዓት ከሚገኘው ገቢ ከ10 በመቶ በላይ የሚሸፍን ሲሆን÷ የኢንዱስትሪ ሰንሰለቱ ዓመታዊ የምርት ዋጋ 12 ትሪሊየን ዩዋን እንደሚያደርሰውም አመላክቷል።

በፈረንጆቹ 2030 የቻይና የሃይድሮጂን ኢነርጂ የገበያ ልኬት 43 ሚሊየን ቶን ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል።

በፈረንጆቹ 2019 ከነበረበት 1 በመቶ አረንጓዴ ሃይድሮጂን የኃይል መጠን ወደ 10 በመቶ እንደሚያድግ እና የገበያው ሚዛንም በ30 እጥፍ እንደሚጨምር ኤጀንሲው መግለፁን ሲጂቲኤን ዘግቧል።

አረንጓዴ ሃይድሮጂን ማለት ከአረንጓዴ እና ከታዳሽ የኃይል ምንጮች ማለትም ከንፋስ እና ከፀሃይ ሃይል ከሚመነጨው ኤሌትሪክ የተገኘ ማለት ነው።

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *