የስራና ክህሎት ሚኒስቴር የስራ ዕድልን ለማስፋት ያለመ ስምምነት ከቶፓን ግራቪቲ ግሩፕ ኩባንያ ጋር ተፈራረመ

የስራና ክህሎት ሚኒስቴር ለስራ አጥ ወገኖች የሥራ ዕድል ለማመቻቸት ያለመ ስምምነት ከቶፓን ግራቪቲ ግሩፕ ኩባንያ ጋር ተፈራረመ።

ስምምነቱን የስራ እና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሀት ካሚል እና የቶፓን ግራቪቲ ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጂን ፒየር ተፈራርመዋል።

ቶፓን ግራቪቲ ተቀማጭነቱን በተባበሩት አረብ ኤሚሬትስ ያደረገ ሲሆን በህትመት ኢንዱስትሪ ላይ የተሰማራ ኩባንያ እና በበርካታ የዓለም አገራት ቅርጫፎች ያሉት ነው።

የስራ እና ክህሎት ሚኒስትር ሙፈሪሀት ካሚል በዚሁ ወቅት እንዳሉት ስራ አጥ ወገኖችን በአገር ውስጥና በውጭ አገራት የስራ ዕድል ተጠቃሚ ለማድረግ እየተሰራ ነው።

በዚሁ መሠረት ቶፓን ግራቪቲ በኢትዮጵያና በተለያዩ የዓለም አገራት ላሉት ኢትዮጵያውያን ወጣቶች የሥራ ዕድል ለማመቻቸት ዛሬ ከኩባንያው ጋር ስምምነት መፈረሙን ተናግረዋል።

ስምምነቱ ለዘላቂ የኢኮኖሚ ዕድገትና የስራ ዕድል ፈጠራ ወሳኝ መሆኑንም ገልጸዋል።

የኩባንያው ማኔጂንግ ዳይሬክተር ጂን ፒየር ለኢትዮጵያውያን የስራ ስልጠናና የስራ ዕድል ተጠቃሚ የሚያደርጉ ስራዎችን እንደሚሰራ ገልጸዋል።

በዲጂታል ኢኮኖሚ ዘርፍና በህትመት ዘርፍ ወጣቶች ክህሎታቸውን እያሳደጉ የስራ ዕድል ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚሰሩ መሆኑንም ጠቁመዋል።

ምንጭ፦ ኢዜአ

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *