ሁለት ዘመናዊ የአውሮፕላን መለዋወጫና ጥገና ማዕከላት ወደ ሥራ ሊገቡ ነው

 የኢትዮጵያ አየር መንገድ ተጨማሪ ሁለት ዘመናዊ የአውሮፕላን መለዋወጫና ጥገና ማዕከላትን ወደ ሥራ ሊያስገባ መሆኑን ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ መስፍን ጣሰው ገለጹ።

የአፍሪካ አቪዬሽን የአውሮፕላን መለዋወጫና ጥገና ተቋማት ኮንፍረንስና ኤግዚቢሽን ትላንት በአዲስ አበባ ተከፍቷል።

ዋና ሥራ አስፈጻሚው አቶ መስፍን ጣሰው በመድረኩ ላይ እንደገለጹት፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ በተያዘው የፈረንጆቹ ዓመት መጨረሻ ተጨማሪ ሁለት ዘመናዊ የአውሮፕላን መለዋወጫና ጥገና ማዕከላትን አገልግሎት ያስጀምራል።

ኢትዮጵያ ተጨማሪ ሁለት ዘመናዊ የአውሮፕላን አካል ክፍሎች ጥገና ኮምፕሌክስና መለዋወጫዎች ማዕከል እየገነባች ነው ያሉት አቶ መስፍን፤ በተያዘው የፈረንጆቹ ዓመት መጨረሻ ወደ አገልግሎት ለማስገባት እየተሠራ ነው ብለዋል።

የአውሮፕላን መለዋወጫና ጥገናው አየር መንገዱን ጨምሮ በአፍሪካ በተለይም በመካከለኛው ምሥራቅ ለሚገኙ አየር መንገዶች አገልግሎት እየሰጠ እንደሚገኝ ጠቅሰው፤ የአየር ፍሬም፣ ሞተርና አካል ጥገናን ጨምሮ የምሕንድስና የቁሳቁስ አገልግሎቶችን እንደሚሰጥ አስረድተዋል።

አፍሪካ አቪዬሽን ኢንዱስትሪ ከሦስት አስርተ ዓመታት በላይ ወሳኝ ሚና ሲጫወት መቆየቱን በመግለጽ፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ግሩፕ ከአፍሪካ አየር መንገድና አምራቾች ጋር ለመተባበር ዝግጁ መሆኑን ገልጸዋል።

በአፍሪካ በቂና አስተማማኝ የአውሮፕላን መለዋወጫና ጥገና አገልግሎት አቅራቢዎች የሉም ያሉት ሥራ አስፈጻሚው፤ የአፍሪካ አየር መንገዶች አውሮፕላኖቻቸውን፣ ሞተሮቻቸውንና አካሎቻቸውን ወደ አውሮፓና መካከለኛው ምስራቅ እየላኩ ይገኛል ብለዋል።

አፍሪካ በአውሮፕላን መሐንዲሶችና ቴክኒሻኖች የሚሠለጥኑ ብዙ ወጣቶች እንደሚኖሩባት ጠቅሰው፤ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ውጤታማና ዘመናዊ የአውሮፕላን መለዋወጫና ጥገና ፋሲሊቲ እየሠራ መሆኑን ጠቁመዋል።

በአፍሪካ አቪዬሽን ኢንዱስትሪ ውስጥ ስትራቴጂ አለመኖር፣ የውስጥ አቅሞች ደካማነት፣ የፋይናንስ አቅርቦት እጥረት መኖሩን በመግለጽ፤ ምቹ የንግድ አካባቢ አለመኖር፣ ከፍተኛ የነዳጅ ዋጋ፣ የመሬት አገልግሎት አቅርቦት፣ ከፍተኛ ግብር፣ የትራፊክ መብት ገደቦች ችግር መሆናቸውን አስረድተዋል።

የትራንስፖርትና ሎጀስቲክስ ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ደንጌ ቦሩ በበኩላቸው፤ ኢትዮጵያ የአቪዬሽን ኢንዱስትሪውን ዕድገትና ልማት በአፍሪካ አህጉር ሁሉ ለማሳደግ ቁርጠኛ ነች።

መድረኩ ምርጥ ተሞክሮዎችን በመለዋወጥ በጋራ ለመሥራት የሚያስችል መሆኑን ጠቅሰው፤ በተለይም ለቀጣዩ ትውልድ የተሻለች አፍሪካን ለመፍጠር እንደሚያስችል ጠቁመዋል።

የአውሮፕላን መለዋወጫና የጥገና አገልግሎት አቅምና ብቃት ለማሳደግ በትብብር መሥራት ያስፈልጋል ያሉት አቶ ደንጌ፤ ኢትዮጵያ የኢንዱስትሪውን ፍላጎት በማሟላት ረገድ ስኬት እያስመዘገበች ነው ብለዋል።

ኢትዮጵያ በአፍሪካ አሕጉርና በተቀረው ዓለም መካከል ወሳኝ ትስስር ሆና እያገለገለች እንደምትገኝ ጠቅሰው፤ የአየር ትራንስፖርት ማዕከል ለመሆን ስትራቴጂያዊ ቦታ ላይ እንደምትገኝ ገልጸዋል።

እንደ አቶ ደንጌ ገለጻ፤ ኢትዮጵያ ለዘላቂ ልማትና ቀልጣፋ የትራንስፖርት ሥርዓት ለመዘርጋት እየተጋች ናት። የኢንዱስትሪውን ዕድገትና ልማት ለማረጋገጥ ከአየር መንገድ ባለድርሻ አካላት ጋር እየተሠራ ነው።

በተጨማሪም የአየር መጓጓዣን ደኅንነት፣ አስተማማኝነትና ቅልጥፍናን ለማረጋገጥ መለዋወጫና ጥገና ወሳኝ ሚና እንዳለው በመግለጽ፤ ለኢኮኖሚ እድገት፣ ለማኅበራዊ ልማትና ለአሕጉራዊ ትብብር ቁልፍ መሆኑንም አመላክተዋል።

በመድረኩ ላይ በዘርፉ የሚሠሩ ግዙፍ ዓለም አቀፍ ተቋማት የልምድ ልውውጥ በማድረግ ሥራዎቻቸውን የሚያቀርቡ ሲሆን ለሦስት ቀናትም እንደሚቆይ ተገልጿል።

ምንጭ፦ (ኢ ፕ ድ)

Leave a Comment

Your email address will not be published. Required fields are marked *